[index]

amharique አማርኛ

police à télécharger



ስለሰብአዊ፡ መብቶች፡ ለማስተማር፡ የሚረዱ፡ አንዳን፡ ዘዴዎች።


በዩኔስኮ፡ ተዘጋጅቶ፡ በኢትዮጵያ፡ ብሄራዊ፡ ኮሚሽን፡ ተተረጎመ


አንቀጽ፡ ፩፤
የሰው፡ ልጅ፡ ሁሉ፡ ሲወለድ፡ ነጻና፡ በክብርና፡ በመብትም፡ እኩልነት፡ ያለው፡ ነው። ፡ የተፈጥሮ፡ ማስተዋልና፡ ሕሊና፡ ስላለው፡ አንዱ፡ ሌላውን፡ በወንድማማችነት፡ መንፈስ፡ መመልከት፡ ይገባዋል።


አንቀጽ፡ ፪፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የዘር፡ የቀለም፡ የጾታ፡ የቋንቋ፡ የሃይማኖት፡ የፖለቲካ፡ ወይም፡ የሌላ፡ ዓይነት፡ አስተሳሰብ፡ የብሔራዊ፡ ወይም፡ የኀብረተሰብ፡ ታሪክ፡ የሀብት፡ የትውልድ፡ ወይም፡ የሌላ፡ ደረጃ፡ ልዩነት፡ ሳይኖሩ፡ በዚሁ፡ ውሳኔ፡ የተዘረዘሩት፡ መብቶችንና፡ ነጻነቶች፡ ሁሉ፡ እንዲከበሩለት፡ ይገባል።

ከዚህም፡ በተቀረ፡ አንድ፡ ሰው፡ ከሚኖርበት፡ አገር፡ ወይም፡ ግዛት፡ የፖለቲካ፡ የአገዛዝ፡ ወይም፡ የኢንተርናሽናል፡ አቋም፡ የተነሳ፡ አገሩ፡ ነጻም፡ ሆነ፡ በሞግዚትነት፡ አስተዳደር፡ ወይም፡ እራሱን፡ ችሎ፡ የማይተዳደር፡ አገር፡ ተወላጅ፡ ቢሆንም፡ በማንኛውም፡ ዓይነት፡ ገደብ፡ ያለው፡ አገዛዝ፡ ሥር፡ ቢሆንም፡ ልዩነት፡ አይፈጸምበትም።


አንቀጽ፡ ፫፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የመኖር፣ ፡ በነጻነትና፡ በሰላም፡ የመኖሩ፡ መጠበቅ፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፬፤
ማንም፡ ሰው፡ ቢሆን፡ በባርነት፡ አይገዛም። ፡ ባርነትና፡ የባሪያ፡ ንግድም፡ በማንኛውም፡ ዓይነት፡ ክልክል፡ ነው።


አንቀጽ፡ ፭፤
ማንም፡ ሰው፡ ቢሆን፡ የጭካኔ፡ ስቃይ፡ እንዳይደርስበት፡ ወይም፡ ከሰብዓዊ፡ አፈጻጸም፡ ውጭ፡ የሆነ፡ የተዋረድ፡ ተግባር፡ ወይም፡ ቅጣት፡ አይፈጸምበትም።


አንቀጽ፡ ፮፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በሕግ፡ ፊት፡ በሰው፡ ዘርነቱ፡ የመታወቅ፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፯፤
ሰው፡ ሁሉ፡ በሕግ፡ ፊት፡ እኩል፡ ነው። ፡ ያለአንዳች፡ ልዩነትም፡ ሕጉ፡ ደህንነቱን፡ እንዲጠበቅለት፡ እኩል፡ የሆነ፡ መብት፡ አለው። ፡ ይህንን፡ ውሳኔ፡ በመጣስ፡ ከሚደረግ፡ ልዩነት፡ ለማድረግ፡ ከሚነሳሳ፡ እንዲጠበቅ፡ ሁሉም፡ የእኩል፡ መብት፡ አለው። ፡


አንቀጽ፡ ፰፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በሕገ፡ መንግስቱ፡ ወይም፡ በሕግ፡ የተሰጡትን፡ መሠረታዊ፡ መብቶች፡ ከሚጥሱ፡ ድርጊቶች፡ ከፍተኛ፡ በሆኑ፡ ብሔራዊ፡ የፍርድ፡ ባለስልጣኖች፡ ፍጹም፡ በሆነ፡ መንገድ፡ እንዲወገድለት፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፱፤
ማንም፡ ሰው፡ ያለፍርድ፡ ተይዞ፡ እንዲታሰር፡ ወይም፡ በግዛት፡ እንዲኖር፡ አይደረግም።


አንቀጽ፡ ፲፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በመብቶቹና፡ በግዴታዎቹ፡ አፈጻጸም፡ እንዲሁም፡ በሚከሰስበት፡ ማንኛውም፡ ዓይነት፡ የወንጀል፡ ክስ፡ ነጻ፡ በሆነና፡ በማያዳላ፡ የፍርድ፡ ሸንጎ፡ በትክክለኛና፡ በይፋ፡ ጉዳዩ፡ እንዲሰማለት፡ የሙሉ፡ እኩልነት፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፲፩፤
፩/፡ በወንጀል፡ ክስ፡ የተከሰሰ፡ ማንኛውም፡ ሰው፡ ለመከላከያው፡ አስፈላጊዎች፡ የሆኑትን፡ ሁሉ፡ አቅርቦ፡ በሚከራከርበት፡ የይፋ፡ ፍርድ፡ ቤት፡ በሕግ፡ መሠረት፡ ወንጀለኛ፡ መሆኑ፡ እስቲረጋገጥበት፡ ድረስ፡ ከወንጀል፡ ነጻ፡ እንደሆነ፡ የመቆጠር፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ማንም፡ ሰው፡ በብሔራዊ፡ ወይም፡ በኢንተርናሽናል፡ ሕግ፡ አንድ፡ ነገር፡ ወንጀል፡ ሆኖ፡ ባልተደነገገበት፡ ጊዜ፡ በፈጸመው፡ ወይም፡ ባልፈጸመው፡ ማንኛውም፡ ሥራ፡ ወንጀለኛ፡ ሆኖ፡ አይከሰስም። ፡ ወይም፡ ወንጀሉ፡ በተፈጸመበት፡ ጊዜ፡ ከተደነገገው፡ ቅጣት፡ ይበልጥ፡ አይፈረድበትም።


አንቀጽ፡ ፲፪፤
ማንም፡ ሰው፡ በግል፡ ኑሮው፡ በቤተሰቡ፡ ውስጥ፡ በቤቱ፡ ወይም፡ በሚጻጻፈው፡ ደብዳቤ፡ በፍርድ፡ ያልተለየ፡ ጣልቃ፡ ገብነት፡ ወይም፡ ክብሩን፡ የሚነካና፡ ስሙን፡ የሚያጎድፍ፡ ተቃውሞ፡ አይፈጸምበትም። ፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ከእንደዚህ፡ ያለ፡ ጣልቃ፡ ገብነት፡ ወይም፡ የሚጎዳ፡ ተግባር፡ ሕግ፡ እንዲከላከልለት፡ መብት፡ አለው። ፡


አንቀጽ፡ ፲፫፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በየብሔራዊ፡ ወሰን፡ ክልሉ፡ የመዘዋወርና፡ የመኖር፡ ነጻነት፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ከማንኛውም፡ አገር፡ ሆነ፡ ከራሱ፡ አገር፡ ወጥቶ፡ እንደገና፡ ወደ፡ አገሩ፡ የመመለስ፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፲፬፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ከጭቆና፡ ሸሽቶ፡ በሌሎች፡ አገሮች፡ ጥገኝነትን፡ የመጠየቅና፡ በደህና፡ የመኖር፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ፖለቲካዊ፡ ካልሆኑ፡ ወንጀሎች፡ ወይም፡ የተባበሩት፡ መንግሥታት፡ ድርጅት፡ ዋና፡ ዓላማዎችን፡ ከሚቃረኑ፡ ሥራዎች፡ የተነሳ፡ በሚደርሱ፡ ክሶች፡ ምክንያት፡ ከሆነ፡ ይህ፡ መብት፡ ሊያገለግል፡ አይችልም።


አንቀጽ፡ ፲፭፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የዜግነት፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ማንም፡ ሰው፡ ያለፍርድ፡ ዜግነቱ፡ አይወሰድበትም፡ ወይም፡ ዜግነቱን፡ የመለወጥ፡ መብት፡ አይነፈገውም።


አንቀጽ፡ ፲፮፤
፩/፡ አካለ፡ መጠን፡ የደረሱ፡ ወንዶችና፡ ሴቶች፡ በዘር፡ በዜግነት፡ ወይም፡ በሃይማኖት፡ ልዩነት፡ ሳይወሰኑ፡ ጋብቻን፡ የመፈጸምና፡ ቤተሰብን፡ የመመሥረት፡ መብት፡ አላቸው፤ ፡ ጋብቻ፡ በመፈጸም፡ በጋብቻ፡ ጊዜና፡ ጋብቻ፡ በሚፈርስበትም፡ ጊዜ፡ እኩል፡ መብት፡ አላቸው።
፪/፡ ጋብቻ፡ የሚፈጸመው፡ ጋብቻ፡ ለመፈጸም፡ በሚፈልጉ፡ ሁለቱም፡ ወገኖች፡ በሚያደርጉት፡ ነጻና፡ ሙሉ፡ ስምምነት፡ መሠረት፡ ብቻ፡ ነው።
፫/፡ ቤተሰብ፡ በኀብረ፡ ሰብ፡ የተፈጥሮና፡ መሰረታዊ፡ ክፍል፡ ስለሆነ፡ በኀብረሰቡና፡ በመንግሥቱም፡ ደህንነቱ፡ እንዲጠበቅለት፡ ይገባል።


አንቀጽ፡ ፲፯፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ብቻውን፡ ወይም፡ ከሌሎች፡ ጋር፡ በኀብረት፡ ሆኖ፡ የኀብረት፡ ባለቤትነት፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ማንም፡ ሰው፡ ያለፍርድ፡ ንብረቱ፡ አይወሰድበትም።


አንቀጽ፡ ፲፰፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የሃሳብ፡ የሕሊናና፡ የሃይማኖት፡ ነጻነት፡ መብት፡ አለው። ፡ ይህም፡ መብት፡ ሃይማኖቱን፡ ወይም፡ እምነቱን፡ የመለወጥ፡ ነጻነትንና፡ ብቻውን፡ ወይም፡ ከሌሎች፡ ጋር፡ በኀብረት፡ በይፋ፡ ወይም፡ በግል፡ ሆኖ፡ ሃይማኖቱን፡ ወይም፡ እምነቱን፡ የማስተማር፣ ፡ በተግባር፡ የመግለጽ፡ የማምለክና፡ የማክበር፡ ነጻነትን፡ ይጨምራል።


አንቀጽ፡ ፲፱፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የሐሳብና፡ ሐሳቡን፡ የመግለጽ፡ መብት፡ አለው። ፡ ይህም፡ መብት፡ ያለጣልቃ፡ ገብነት፡ በሐሳብ፡ የመጽናትንና፡ ዜናን፡ ወይም፡ ሐሳቦችን፡ ያላንዳች፡ የድንበር፡ ገደብ፡ የማግኘትን፡ የመቀበልንና፡ ወይም፡ የማካፈልን፡ ነጻነትም፡ ይጨምራል።


አንቀጽ፡ ፳፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በሰላም፡ የመሰብሰብና፡ ግንኙነት፡ የማድረግ፡ ነጻነት፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ማንም፡ ሰው፡ የአንድ፡ ማኀበር፡ አባል፡ እንዲሆን፡ አይገደድም።


አንቀጽ፡ ፳፩፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በቀጥታ፡ ወይም፡ ነጻ፡ በሆነ፡ መንገድ፡ በተመረጡ፡ እንደራሴዎች፡ አማካኝነት፡ በአገሩ፡ መንግስት፡ የመካፈል፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በአገሩ፡ የህዝብ፡ አገልግሎት፡ እኩል፡ የማግኘት፡ መብት፡ አለው።
፫/፡ የመንግስት፡ ሥልጣን፡ መሠረቱ፡ የሕዝቡ፡ ፈቃድ፡ መሆን፡ አለበት። ፡ ይህም፡ ፈቃድ፡ ለሁሉም፡ እኩል፡ በሆነ፡ በምሥጢር፡ በሚደረግ፡ የድምፅ፡ መስጠት፡ ምርጫ፡ ወይም፡ በተመሳሳይ፡ ሁኔታ፡ በየጊዜውና፡ በትክክል፡ በሚፈጸሙ፡ ምርጫዎች፡ እንዲገለጽ፡ መሆን፡ አለበት።


አንቀጽ፡ ፳፪፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የኀብረ፡ ሰብ፡ አባል፡ እንደመሆኑ፡ በኀብረ፡ ሰብ፡ ደህንነቱ፡ እንዲጠበቅ፡ መብት፡ አለው። ፡ እንዲሁም፡ በብሔራዊ፡ ጥረትና፡ በኢንተርናሽናል፡ መተባበር፡ አማካይነትና፡ በእያንዳንዱ፡ መንግስት፡ ድርጅትም፡ የሀብት፡ ምንጮች፡ መሰረት፡ ለክብሩና፡ ለሰብዓዊ፡ አቅሙ፡ ነጻ፡ እድገት፡ የግድ፡ አስፈላጊ፡ የሆኑት፡ የኤኮኖሚ፡ የማኀበራዊ፡ ኑሮና፡ የባህል፡ መብቶች፡ በተግባር፡ እንዲገለጹለት፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፳፫፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የመሥራት፡ የሥራ፡ ነጻ፡ ምርጫና፡ ለሥራም፡ ትክክለኛና፡ ተስማሚ፡ የአሠራር፡ ሁኔታዎችና፡ ሥራም፡ እንዳያጣ፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ያላንዳች፡ ልዩነት፡ ማድረግ፡ ለአንድ፡ ዓይነት፡ ሥራ፡ እኩል፡ የሆነ፡ ደመወዝ፡ የማግኘት፡ መብት፡ አለው።
፫/፡ በሥራ፡ ላይ፡ ያለ፡ ሰው፡ ለእራሱና፡ ለቤተሰቡ፡ ለሰብዓዊ፡ ክብር፡ ተገቢ፡ የሆነ፡ ኑሮን፡ የሚያስገኝለትና፡ ካስፈለገም፡ በሌሎች፡ የኀብረሰብ፡ ደህንነት፡ መጠበቂያ፡ ዘዴዎች፡ የተደገፈ፡ ትክክለኛና፡ ተስማሚ፡ ዋጋውን፡ የማግኘት፡ መብት፡ አለው።
፬/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ጥቅሞቹን፡ ለማስከበር፡ የሙያ፡ ማኀበሮችን፡ ለማቋቋምና፡ ማኀበርተኛ፡ ለመሆን፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፳፬፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የዕረፍትና፡ የመዝናናት፡ እንዲሁም፡ በአግባብ፡ የተወሰኑ፡ የሥራ፡ ሰዓቶች፡ እንዲኖሩትና፡ በየጊዜው፡ የዕረፍት፡ ጊዜያትን፡ ከደመወዝ፡ ጋር፡ የማግኘት፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፳፭፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ለእራሱና፡ ለቤተሰቡ፡ ጤንነትና፡ ደህንነት፡ ምግብ፣ ፡ ልብስ፣ ፡ ቤትና፡ ሕክምና፡ አስፈላጊ፡ የማኀበራዊ፡ ኑሮ፡ አገልግሎቶችም፡ ጭምር፡ የሚበቃ፡ የኑሮ፡ ደረጃ፡ ለማግኘት፡ መብት፡ አለው። ፡ ሥራ፡ ሳይቀጠር፡ ቢቀር፡ ቢታመም፡ ለመሥራት፡ ባይችል፡ ባል፡ ወይም፡ ሚስት፡ ቢሞት፡ ቢያረጅ፡ ወይም፡ ከቁጥጥሩ፡ ውጭ፡ በሆኑ፡ ምክንያቶች፡ መሰናከል፡ ቢገጥመው፡ ደህንነቱ፡ እንዲጠበቅለት፡ መብት፡ አለው።
፪/፡ ወላድነትና፡ ሕጻንነት፡ ልዩ፡ ጥንቃቄና፡ እርዳታ፡ የማግኘት፡ መብት፡ አላቸው፤ ፡ በጋብቻ፡ ወይም፡ ያለጋብቻ፡ የሚወለዱ፡ ሕጻናትም፡ የተመሳሳይ፡ የደህንነታቸው፡ መጠበቅ፡ መብት፡ አላቸው።


አንቀጽ፡ ፳፮፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የመማር፡ መብት፡ አለው። ፡ ትምህርት፡ ቢያንስ፡ ቢያንስ፡ በአንደኛ፡ ደረጃና፡ በመሰረታዊ፡ ደረጃዎች፡ በነጻ፡ ሊሆን፡ ይገባል። ፡ የአንደኛ፡ ደረጃ፡ ትምህርት፡ መማር፡ ግዴታ፡ ነው። ፡ የቴክኒክና፡ የልዩ፡ ልዩ፡ ሙያ፡ ትምህርት፡ በጠቅላላው፡ የከፍተኛ፡ ደረጃ፡ ደግሞ፡ በችሎታ፡ መሠረት፡ ለሁሉም፡ እኩል፡ መሰጠት፡ አለበት።
፪/፡ ትምህርት፡ ለእያንዳንዱ፡ ሰው፡ ሁኔታ፡ ማሻሻያና፡ ለሰብዓዊ፡ መብቶችም፡ መሠረታዊ፡ ነጻነቶች፡ ክብር፡ ማዳበርያ፡ የሚውል፡ መሆን፡ አለበት። ፡ እንዲሁም፡ የተለያየ፡ ዘር፡ ወይም፡ ሃይማኖት፡ ባሏቸው፡ ሕዝቦች፡ መካከል፡ ሁሉ፡ መግባባትን፡ ተቻችሎ፡ የመኖርንና፡ የመተባበርን፡ መንፈስ፡ የሚያጠነክርና፡ የተባበሩት፡ መንግሥታት፡ ድርጅት፡ ሰላምን፡ ለመጠበቅ፡ የሚፈጽማቸው፡ ተግባሮች፡ እንዲስፋፋ፡ የሚያበረታቱ፡ መሆን፡ አለበት። ፡
፫/፡ ወላጆች፡ ለልጆቻቸው፡ ለመስጠት፡ የሚፈልጉትን፡ ትምህርት፡ ለመምረጥ፡ የቅድሚያ፡ መብት፡ አላችው። ፡


አንቀጽ፡ ፳፯፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በኀብረ፡ ሰቡ፡ የባህል፡ ኑሮ፡ በነጻ፡ መካፈልና፡ በኪነ፡ ጥበብ፡ ለመጠቀም፡ በሳይንስ፡ እርምጃና፡ በጥቅሞቹም፡ ለመሳተፍ፡ መብት፡ አለው። ፡
፪/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ ከደረሰው፡ ማንኛውም፡ የሳይንስ፡ የድርሰትና፡ የኪነ፡ ጥበብ፡ ሥራ፡ የሚያገኘው፡ የሞራሉንና፡ የሃብት፡ ጥቅሞች፡ እንዲከበሩለት፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፳፰፤
እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በዚህ፡ ውሳን፡ ውስጥ፡ የተዘረዘሩት፡ መብቶችና፡ ነጻነቶች፡ በሙሉ፡ በተግባር፡ እንዲውሉ፡ ለሚደረግባቸው፡ የኀብረሰብና፡ የኢንተርናሽናል፡ ሥርዓት፡ የመጠቀም፡ መብት፡ አለው።


አንቀጽ፡ ፳፱፤
፩/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ የራሱ፡ ነጻነትና፡ ሙሉ፡ መሻሻል፡ በሚያገኝበት፡ ኀብረሰብ፡ ውስጥ፡ የሚፈጽማቸው፡ ግዴታዎች፡ ይኖሩበታል።
፪/፡ እያንዳንዱ፡ ሰው፡ በመብቶቹ፡ በነጻነቶቹ፡ በሚጠቀምበት፡ ጊዜ፡ የሚታገደው፡ የሌሎችን፡ መብቶችና፡ ነጻነቶች፡ በሚገባ፡ ለማሰከበር፡ ብቻ፡ በተደነገጉ፡ ሕጎችና፡ የግብረ፡ ገብነትን፡ የጠቅላላውን፡ ሕዝብ፡ ፀጥታና፡ ደህንነት፡ በዴሞክራቲክ፡ ማኀበራዊ፡ ኑሮ፡ ትክክለኛ፡ የሆነው፡ ተፈላጊ፡ ጉዳይ፡ ለማርካት፡ በተወሰነው፡ ብቻ፡ ነው።
፫/፡ እነዚህ፡ መብቶችና፡ ነፃነቶች፡ በማንኛውም፡ ሁኔታ፡ የተባበሩት፡ መንግሥታት፡ ድርጅት፡ መሰረት፡ ዓላማዎች፡ ተቃራኒ፡ በሆነ፡ መንገድ፡ ሊፈጸሙ፡ አይገባቸውም።


አንቀጽ፡ ፴፤
በዚህ፡ ውሳኔ፡ ከላይ፡ የተዘረዘረው፡ ሁሉ፡ በዚሁ፡ ውስጥ፡ የተጠቀሱትን፡ ማናቸውም፡ መብቶች፡ ወይም፡ ነጻነቶች፡ ለማበላሸት፡ በታሰበ፡ ማንኛውም፡ ዓይነት፡ ተግባር፡ ለማዋል፡ ወይም፡ ድርጊትን፡ ለመፈጸም፡ ለማንኛውም፡ መንግሥት፡ ወይም፡ ድርጅት፡ ወይም፡ ሰው፡ የተባሉ፡ አይተረጎሙም።
[index]